የኢትዮጵያ ብዝሀ ሕይወት ኢንስቲትዩት ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የአካባቢ ሳይንስ ማዕከል ጋር ጥር 29 ቀን 2017 ዓ.ም በኢንስቲትዩቱ መሰብሰቢያ አዳራሽ የመግባቢያ ሰነድ ተፈራረመ፡፡
ዶ/ር መለሰ ማርዮ የኢትዮጵያ ብዝሀ ሕይወት ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ባደረጉት የመክፈቻ ንግግር የኢንስቲትዩቱን አጠቃላይ የስራ እንቅስቃሴ መረጃ ያቀረቡ ሲሆን የብዝሀ ሕይወት ጥፋትን በጋራ መከላከል ተገቢ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
አያይዘውም የጀነቲክ ሀብቶችን በመጠበቅ የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ እንደሚገባ አስታውሰው የመግባቢያ ሰነዱ የሚያተኩርባቸውን ይዘቶች አቅርበዋል፡፡
ፕሮፌሰር አህመድ ሁሴን የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የአካባቢ ሳይንስ ማዕከል ኃላፊ በበኩላቸው የማዕከሉን አጠቃላይ የስራ እንቅስቃሴ፣ ስኬቶች፣ ሀገራዊና ዓለምአቀፋዊ እንቅስቃሴዎችን ዘርዝረው የትምህርት ተቋማት ከምርምር ተቋማት ጋር በጋራ የመስራትን ጥቅሞች ጠቅሰዋል፡፡
ዶ/ር ገመዶ ዳሌ በበኩላቸው የአካባቢ ጥበቃና የብዝሀ ሕይወት ጥበቃ ስራዎችን ከውሳኔ ሰጪዎች ጋር በመወያየት ያሉ ተግዳሮቶችን ተፈጥሮን መሰረት ባደረገ መፍትሄ መፍታት እንደሚገባ ጠቁመዋል፡፡
ከመግባቢያ ሰነዱ ፊርማ ሥነ-ሥርዓት በኋላ ሁለቱም አካላት የነገዋን ኢትዮጵያ ታሳቢ በማድረግ የአካባቢ ጥበቃና የብዝሀ ሕይወት ጥበቃ ስራዎችን በጋራ ለማከናወን ሲስማሙ ኢንስቲትዩቱን የመጎብኘት ሥነ-ሥርዓትም ተከናውኖ ፕሮግራሙ ተጠናቋል፡፡



